(EMF) በሃረር ከተማ ውስጥ አለመረጋጋት ተፈጥሯል:: ዋናው ምክንያት ከትላንት በስትያ በተለምዶ “መብራት ሃይል” ተብሎ በሚጠራው ህንጻ ላይ የተነሳው ቃጤሎ ነው:: የእሳቱ መነሻ… ራሱ መንግስት ነው የሚሉት ሰዎች ተቃውሟቸውን የዚያኑ እለት አሰምተዋል:: ይህንን ተቃውሞ ተከትሎ ከተማዋ በተኩስ ድምጽ ስትናወጥ ቆይታለች:: ከዚያው ጋር ተያይዞ, ዜጎችን መደብደብ እና ማሰር ክልሉን የሚያስተዳድሩት ሃረሪዎች የስራ ድርሻ ሆኖ ነበር የቆየው::
በሃረር ከተማ ውስጥ ጉልህ የሆነ የዘር መድልዎ ይደረጋል:: እንደወትሮው መስቀል ደመራ ጥምቀት ማድረግ ብዙም አይታሰብም:: የአማራ ዝርያ እና የኦርቶዶክስ እምነት ተከታዮች የሚገፉበት ከተማ ነው:: ከዚያም አልፎ በኦሮሞ ተወላጆችም ላይ ተመሳሳይ ተጽዕኖ ይደረጋል:: ይህ የእሳት ቃጠሎ ከመነሳቱ በፊት የሃረሪ ተወላጆች በዚያ ገበያ ስፍራ የሚገኙ ሱቆቻቸውን ሲሸጡ እንደነበርና በአንደኛው ሱቅ ውስጥ ብዙ ተቀጣጣይ ጋዝ ሲቀመጥ ነበር ተብሏል:: ውጭ አገር በሚገኙ የቀድሞ የከተማው ነዋሪዎች የተገዛው የእሳት አደጋ መኪናም በቂ ውሃ አለመርጨቱን ነው – ታዛቢዎች የሚናገሩት::
በሃረር ከተማ ውስጥ ያለውን ወቅታዊ ችግር ለማስረዳት በሃረር ነዋሪ የሆነ አንድ ወጣት.. ለጋዜጠኛ አቤ ቶኪቻው የጻፈውን ደብዳቤ መመልከት ጠቃሚ ነው:: እንዲህ ሲል ነበር ደብዳቤውን የጻፈለት::“አቤ ዛሬ ይህን ጽሁፍ የምጽፍልህ ከመንግስትም ሆነ ከተበዳይ ወግኜ አይደለም፡፡ ትውልዴ አና እድገቴ አዛው ሀረርጌ ነው ነገር ግን ለትህምርት ወደ አዲስ አበባ ከመጣሁ ሰነባብቻለሁ፡፡ በቅርብ እንደሰማነው የሀረር መብራት ሀይል ገበያ ላይ በተነሳው እሳት ምክንያት ምስኪኑ ህዝባችን ለምን የሚለውን ጥያቄ ለማቀረብ ሰለፍ እንደወጣ ሰምተናል አይተናል፡፡ ነገር ግን ዛሬ ሀረር ለየት ያለ ክስተት አጋጥሟታል ፡፡ በትላንትናው ቀን ለሰልፍ የወጡ ወጣቶችን በካሜራ ቀርጸው ዛሬ ከ400 በላይ ወጣቶችን አፍሰው ወህኒ ከተዋል፡፡
“የክልሉ መንግስት በአማራዎቸ አና በአሮሞዎች ላይ ከባድ ጥላቻ አለበት፡፡ ሀደሬ ካለሆንክ መንኛውም አይነት ማህበራዊም ሆነ ፖለቲካዊ አገልግሎቶች ቅድሚያ አታገኝም፡፡ ወጣት ነኝ፣ 20 አመቴ ነው፣ ነገር ግን አዝች መሬት ላይ ከ እንደዚ አይነት መንግስት ጋር መኖር መሮኛል፡፡ ከኔ ያንተ ድምጽ ከፍ ይላል በዬ ነው የምጽፍልህ… ማንነቴ ካንተ ባያልፍ ደስ ይለኛል፡፡ የሰጠሁክን መረጃ ያገኘሁት ሀረር ከሚኖር የሱቅ ነጋዴ ከሆነው አጎቴ ነው፡፡
ሰላም ሰንብት!”
ከላይ የገለጽነውን ደብዳቤ የላከው ነዋሪነቱ በሃረር የሆነ ወጣት ሲሆን; አሁን በከተማው ያለውን ችግር እና ውጥረት በከፊል የሚያሳይ ነው:: ከትላንት ጀምሮ ጉዳያቸውን ለማስረዳት ወደ ክልሉ ሃላፊዎች የሄዱ ተጎጂዎች የተረፋቸው ነገር; መታሰር ሆኗል:: የክልሉ አስተዳዳሪ አቶ ሙራድ አብዱላሂም ቢሆኑ ሰዎች መታሰራቸውን አልካዱም:: በአሁኑ ወቅት ከሰላሳ በላይ ወጣቶች መታሰራቸውን የቅርብ ምንጮች ይናገራሉ:: በሞት እና በህይወት መሃል ሆነው ወደ ሆስፒታል የተወሰዱትም ብዙ ናቸው:: የሃረር የሰሞኑ ውሎ ይህን ይመስል ነበር::