Wednesday, 7 May 2014

በእስር ላይ የሚገኙት የሰማያዊ ፓርቲ አባላት ላለፉት ቀናት ሲያካሂዱ የነበረውን የረሀብ አድማ ዛሬ በፕ/ር መስፍን ወልደማርያም አማላጅነት እንዲያቆሙ ተደረገ፡፡

May 6, 2014
በእስር ላይ የሚገኙት የሰማያዊ ፓርቲ አባላት ላለፉት ቀናት ሲያካሂዱ የነበረውን የረሀብ አድማ ዛሬ በፕ/ር መስፍን ወልደማርያም አማላጅነት እንዲያቆሙ ተደረገ፡፡
ፕ/ር ለእስረኞቹ፣ ስርዓቱ የያዙትን መንገድ እንደማይረዳው እና እንዲህ አይነት ትግል የሚሰራው መጀመሪያ የሰብዓዊነት ትርጉም እና ክብር የሚገባው ስርዓት ሲኖር እንደሆነ አስረድተው እስር ቤት ውስጥ ሆነው ከሚታገሉ ወጥተው እንዲታገሉ በመምከር ቢያንስ አሁን ምግብ እንዲወስዱ አሳምነው ይዘውት የመጡትን ቸኮሌቶች እንዲመገቡ አድርገዋል፡፡
6 የሰማያዊ ፓርቲ አመራር እና አባላት ላለፉት ሁለት ሳምንታት ያለምንም ክስ በእስር እየማቀቁ ሲሆን በርካቶችም ከፍተኛ ድብደባ ተፈጽሞባቸል ፡፡ በተለይ ወጣት ዮናስ ከድር ፈተና እንዳይፈተን ከመከልከሉም በላይ በደረሰበት ከፍትኛ ድብደባ መንቀሳቀስ እንደማይችል መዘገቡ ይታወሳል፡፡
(በፎቶው ላይ የምታዩት የፓርቲው የምክር ቤት ሰብሳቢ አቶ የሽዋስ አሰፋ በረሀብ አድማው ምክንያት ታሞ ከሆስፒታል መልስ በፖሊስ ጣቢያው በር ላይ እጁ በካቴና እንደታሰረ ፕ/ር መስፍን ሲያነጋግሩት)
Blue Party Ethiopia

የአንድነት ፓርቲ አመራሮች የሰማያዊ ፓርቲ አባላት ሰላማዊ ሰልፍ እንዳይሳተፉ መከልከል ብዙዎችን አስቆጥቷል

May 7, 2014
“የሰማያዊ ፓርቲ አባላት አንድነት የጠራውን የሰላማዊ ሰልፍ እንደሚቀላቀሉ አስታወቁ” የሚለው ዜና ለውጥ ናፋቂዎችን በእጅጉ ያስደሰተ ነበር። ይሁንና አንድነት ፓርቲ ሚያዝያ 26 ቀን 2006 ዓ.ም በአዲስ አበባ “የእሪታ ቀን” በሚል ባካሄደው ሰላማዊ ሰልፍ ላይ ትንታጎቹ የሰማያዊ ወጣቶች አልታዩም። ከሞላ ጎደል ከዚህ በታች የተለያዩ የሰማያዊ ፓርቲ አባላት ስለሁኔታው የገለጹትን ለአንባብያን ለማካፈል ሞክረናል።
———————————–
በአንድነት ፓርቲ አዝኛለው
Brhanu Tekleyared, Semayawi party public relation
ብርሃኑ ተክለያሬድ
በጣም ከፍቶኛል በጣም አዝኛለሁ በፖለቲካ ህይወቴ ብዙ ነገር ደርሶብኛል እንደዛሬው ግን ከፍቶኝ አያውቅም፡፡ነፍስ ካወቅኩ ጀምሮ ያለቀስኩበት ቀን ከ2 ጊዜ አይዘልም ዛሬ ግን ጓደኞቼ እስከሚገረሙብኝ ድረስ ስቅስቅ ብዬ አልቅሻለሁ።
እንደ ሌባ “ከዚህ ሰልፍ ውጡ” ተብለን ስንወጣ የተሰማኝ ስሜት……ግን ይሄ መንገድ የት ያደርሳል?
————————————-
በአንድነት ፓርቲ አዝኛለው
ትላትና የሰማያዊ ፓርቲ የወጣቶች ጉዳይ ባዘጋጀው ፕሮግራም ታሪካዊ ውሳኔ ተላልፏአል፡፡ የውሳኔው ዋና ሃሳብ አንድነት ፓርቲ ባዘጋጀው ፕሮግራም ላይ በመገኘት ፓርቲው ባነሳው ህዝባዊ ጥያቄ በጋር በመቆም አጋርነት ለማሳየት ነው፡፡ በመሆኑም እኔን ጨምሮ ቁጥራችን ቀላል የማንባል የሰማያዊ ፓርቲ አባላቶች እና አመራሮች በሰልፉ ላይ ለመገኘት ዝግጅታችንን በሚገባ ተወጥተን በቦታው ተገኝተን ነበር፡፡ ግን አንድነት ፓርቲ በሰልፉ ላይ እንዳንሳተፍ ክልከላ አደረገብን፤ዋንኛው ምክንያትም ደግሞ
1. የሰማያዊ ፓርቲ አርማ ይዞ መገኘት እና ቲሸርት መልበስ አይቻልም
2. በእናንተ ምክንያት ፖሊስ እንዲያስረን አንፈልግም
3. ሰልፉ የሰማያዊ ሳይሆን የአንድነት ነው፤ እናተ መገኘት አትችሉም፡፡ እና የመሳሰሉትን ምክንያት በመስጠት በሰልፉ ላይ እንዳንገኝ ተደርገናል፡፡
ይሄን ቅረታዬን በማህበራዊ ድረ-ገፅ ከመልቀቄ በፌት የፓርቲው ከፍተኛ አመራሮች ለሆኑት
Yidnekachew Kebede, Semayawi party leadership member
ይድነቃቸው ከበደ
1. ለአቶ አብታሙ አያሌው
2. ለአቶ ዳንኤል ተፈራ
3. ለአቶ ተክሌ በቀለ
4. ኢ/ር ዘለቀ ረዲ በአካል እና በስልክ አናግሪያቸዋለው፡፡
የሰጡኝ ምላሽ ግን ከተጠያቂን ለመዳን አንዱ በሌላው ላይ ምክንያት ከመስጠት ያለፍ ተገቢ ምላሽ አላገኘሁም ፡፡ በተለይ አቶ ዳዊት ሰለሞን እና ዳዊት አስራደ ፍፁም ጨዋነት በጎደለው መልኩ ምላሽ ሲሰጡ የነበረት ፡፡
ከምንም በላይ ግን በሰልፉ ለመገኘት እንዲሁም ሰልፉ ላይ መሳትፍ አትችሉም ሲባል እጅግ በሚያስደንቅ ጨዋነት ትብብራቸውን ላሳዩ የምንግዚም ምርጥ ሰላማዊ ታጋይ ለሆኑት የሰማያዊ ፓርቲ ጎዶች አክብሮቴ የበለጠውን እንዲጨምር ሆኗአል፡፡
——————————————
ማን ያውራ? የነበረ!
ስለዛሬው የአንድነት ሰልፍና የሰማያዊዎች መባረር ሙሉውን መረጃ እነሆ፡፡
ሚያዚያ 19 የተደረገውን የፓርቲዬን የሰማያዊን ሰልፍ እስር ቤት በመሆኔ ምክንያት መገኘት ባለመቻሌ አዝኜ ነበር፡፡ ምናልባትም የአንድነት ሰልፍ ከመደረጉ በፊት ከእስር ቤት የምወጣ ከሆነ ሰልፉን በግሌ ለመሳተፍ ለራሴ ወስኜ ነበር፡፡ ከሌሎች አብረን ከታሰሩ ጓዶቼ ጋርም ስንነጋገር ከተፈቱ በሰልፉ ላይ ለመገኘት እንደሚፈልጉ አጫውተውኝ ነበር፡፡ እንደጠበቅነውም አልቀረም ከ10 ቀን የእስር ቤት ቆይታ በኋላ አርብ ምሽት ከእስር ተፈታን:: ቅዳሜ እለት የተካሄደውን የሰማያዊ ወጣቶች ውይይት ባልካፈልም የተወሰነውን ስሰማ ግን በጣም ደስ ብሎኝ ነበር፡፡ እናም ዛሬ እሁድ በማለዳ በአንደነት ሰልፍ ላይ ለመገኘት ቁርስ እንኳን ከአፌ ሳላደርስ ነበር ወደ ቀበና የገሰገስኩት፡፡
ቀበና ደርሼ ከታክሲ እንደወረድኩኝ ፊትለፊት ያየሁት ጥላዬ ታረቀኝን ነበር፡፡ ለሰላምታ ወደ እርሱ ስጠጋ ያሳየኝ ፊት ግር ቢለኝም ልጁ ምን ሆኖ ነው ከማለት ያለፈ ሌላ ነገር ይኖረዋል ብዬ አልጠበኩም ነበር፡፡ የሆነው ሆኖ አንድነት ቢሮ የደረስኩት እጅግ በጠዋት ነበር (ምናልባትም ካላጋነንኩት ከአንዳንዶቹ የሰልፉ አስተባባሪዎችም በፊት)፡፡ ቢሮው በር ላይ ሆኜ የሰማያዊን ልጆች መምጣትና የሰልፉን መጀመር በጉጉት መጠባበቅ ያዝኩኝ፡፡ በግምት ሰልፉ ሊጀመር ግማሽ ሰአት ያህል ሲቀረው የሰማያዊ ፓርቲ ህዝብ ግንኙነት እና ሌሎችም የሰማያዊ ወጣቶች ጥሩምባቸውን እያሰሙ መጡ፡፡ የህዝቡ አቀባበል አሁንም ድረስ በአይነ ህሊናዬ ይታየኛል፡፡ ጭብጨባው፣ ሰላምታው፣ አድናቆቱ ለጉድ ነበር፡፡
Eyasped Tesfaye, Semayawi party member
ኢያስፔድ ተሰፋዬ
ብርሀኑና ሌሎችም ጓደኞቼን ሰላም ካልኩኝ በኋላ ትኩረት እንዳንስብ ወደ ጥግ ላይ እንሁን ተባብለን ጥጋችንን ለመያዝ ወደበሩ እየሄድን ሳለ ዳዊት ሰለሞን ብርሀኑን ብሎ ተጣራና በእጅ ምልክት እንዲመጣ ነገረው፡፡ እኛም ምናልባት የሰልፍ አስተባባሪ ባጅ ሊሰጠው ይሆናል ተባብለን ወደታች ወርደን ቆምን፡፡ ጉዳዩ ግን ሌላ ነበር፡፡ ብርሀኑ ዳዊት ሰለሞን ወይ ቲሸርታችሁን አውልቁ ወይ ሂዱልን ብሏልና ምን ይሻላል አለን? እኔም ዳዊት የሚባለው ግለሰብ በተደጋጋሚ በፌስቡክ ላይ የሚለጥፋቸውን መረን የወጡ አስተያየቶች ስላየሁኝ ልጁ ችግር ስላለበት ነው እስቲ መጀመሪያ እኔ ላናግረው ብዬ ወደ ውስጥ ገባሁ፡፡
ወደ ውስጥ ስገባ አቶ ዳንኤል ተፈራና አቶ ግርማ ሰይፉን ቆመው እያወሩ ስላየኋቸው በቀጥታ ወደ እነርሱ በማምራት ለዳንኤል ‹‹እየሆነ ያለው ነገር ምንድነው? ለምንድነው ዳዊት ሰለሞን የሰማያዊን ቲሸርት አውልቁ ወይ ሂዱ የሚለው? በእኛ ሰልፍ ላይ የእናንተ ልጆች የሚሊዮኖች ድምፅ ለነፃነት የሚል ቲሸርት ለብሰው ሲሰለፉ እኛ እኮ ምንም አላልንም ነበር›› አልኩት! ምንም ሳልጨምር እና ሳልቀንስ ዳንኤል የሰጠኝ መልስ ግን ‹‹ትናንት ምሽት በፌስቡክ ላይ የለቀቃችሁትን አይቻለሁ ሞቲቫችሁ ጥሩ አይደለም፡፡ የእናንተን ባነር ምናምን ይዛችሁ የአንድነት ሰልፍ ላይ መሳተፍ አትችሉም›› የሚል ነበር፡፡ በንግግሩ ስላዘንኩኝ ምንም መልስ ሳልሰጠው ወደ ደጅ ወጣሁ፡፡
ደጅ ላይ ኢ/ር ዘለቀ ረዲ፣ ተክሌ በቀለ፣ አስራት አብርሀ፣ ዳዊት አስራደ እና ድንቁ(ስማቸውን እርግጠኛ አይደለሁም፤ሸምገል ያሉ ሰውዬ) ቆመው እነ ብርሀኑን ሲያናግሩዋቸው ስላየሁ ወደዚያው አመራሁ፡፡ ስደርስ የሰማሁት ነገር ግን ፈፅሞ ያልጠበኩት ነገር ነበር፡፡ አቶ ድንቁ ‹‹ባለፈው ጊዜ በእናንተ ሰልፍ ላይ እንደነበረው አይነት ከፖሊስ ጋር ግጭት ውስጥ መግባት አንፈልግም፡፡ በእናንተ ምክንያት መታሰር አንፈልግም›› ሲሉ ብርሀኑ ተ/ያሬድ ‹‹እኛ ችግር ፈጣሪዎች ከሆንባችሁ መሄድ እንችላለን ግን እኛ ለፓርቲዎች ተባብሮ መስራት ይሄ አንድ ጥሩ ጅምር ይሆናል ብለን አስበን ነበር›› ሲል ዳዊት አስራደ ከአፉ ተቀብሎ ‹‹መጀመሪያ በጠረጴዛ ዙሪያ ተነጋገር እንጂ በሰው ሰልፍ ላይ በመገኘት አይደለም….ወዘተ ›› እያለ ሲናገር ከዚህ በላይ ቆሞ መስማቱ አላስፈላጊ ስለነበር በቃ ቻው ብለን ተሰናብተን ሰልፈኛውን ላለመረበሽ በሚል በታችኛው መንገድ ሄድን፡፡
ከአካበቢው እስክንርቅ ድረስ ግን ከጀርባችን የነበረው ሰው ለምን ይሄዳሉ እያለ ሲጠይቅ ይሰማን ነበረ፡፡ የሆነው ሁሉ ፈፅሞ ከጠበኩት ውጪ ነበር፡፡ ሰልፉን ለመቀላቀል ግሪን ቫሊ ካፌ ውስጥ ቁጭ ብለው ይጠባበቁ የነበሩት ሌሎች ጓዶቻችን ጋር በማምራት የተፈጠረውን ነገር አስረዳናቸው፡፡ ሁኔታውን ማመን ያቃተው የሰማያዊ ፓርቲ የህግ ጉዳይ ሀላፊ ይድነቃቸው ከበደ ሁለት ሰዎች ጋር ስልክ ደወለ፡፡ መጀመሪያ ሀብታሙ አያሌው ጋር፡፡ ሀብታሙ ‹‹እኔ ቢሮ አልነበርኩም እንዲህ ያለ ነገር መፈጠሩንም አላወኩም›› ሲል ሽምጥጥ አድርጎ ካደ(ትዝብት አንድ!) ቀጥሎ ዳንኤል ተፈራ ጋር ደወለ፡፡ ዳንኤልም ‹‹ምንም የማውቀው ነገር የለም፡፡ ያናገረኝም ሰው የለም›› ሲል ካደ(ትዝብት ሁለት!) ይድነቅ ኢያስፔድ የሚባል የእኛ ልጅ አላናገረህም ወይ ብሎ በድጋሚ ሲጠይቀውም ዳንኤል ‹‹ያናገረኝ የለም›› ሲል መልስ ሰጠ፡፡ ይህን ጊዜ እኔ ይድነቅ እና አፉወርቅ በመሆን በድጋሚ ወደ አንድነት ቢሮ አመራን፡፡ በዚህኛው ዙር ደግሞ አቶ ተክሌን፣ ኢ/ር ዘለቀ ረዲን፣ ዳዊት አስራደን እና ዳንኤል ተፈራን መንገድ ላይ አግኝተን ለምን እንዲህ ይደረጋል የሚል ጥያቄ ስንጠይቃቸው በቅን መንፈስ ያናገረን ዘለቀ ረዲ ብቻ ነበር፡፡ ዳንኤል ተፈራ ያናገረኝ የለም የሚለው ውሸቱ አሳፍሮት መሰለኝ ሊያናግረን እንኳን ፈቃደኛ ሳይሆን ትቶን ወደ ሰልፉ ውስጥ ገባ፡፡ ተክሌ በቀለም ቢሆኑ ከሰልፉ በኋላ እንነጋገራለን መጋጨት የለብንም ምናምን እያሉ እንደቸኮለ ሰው በመሆን ወደ ሰልፉ ተቀላቀሉ፡፡ ዳዊት አስራደ ግን እስመጨረሻው ድረስ በእኛ ሴረሞኒ ላይ የራሳችሁን ቲሸርት ለብሳችሁ መገኘት አትችሉም ሂዱልን ሲለን ነበር፡፡ ከሁሉም በላይ ግን ልቤን የሰበረው አፉወርቅ ‹‹የኢህአዴግን ቲሸርት አድርጌ ብመጣ ታባርረኛለህ ወይ›› ብሎ ዳዊትን ሲጠይቀው የሰጠው መልስ ነበር፡፡ ዳዊት ‹‹የኢህአዴግን ቲሸርት ለብሰህ ብትመጣ እቀበልሀለሁ፡፡ እናንተ እኮ በይፋ ሪኮግኒሽን ነስታችሁናል፡፡ ኢህአዴግ ያንን አላደረገም፡፡ መጀመሪያ በጠረጴዛ ዙሪያ ችጋራችንን መፍታት አለብን›› የሚል ነበር፡፡ በእውነት ግን ለአንድነት ፓርቲ ከሰማያዊ እና ከኢህአዴግ ማን ይቀርባል? ይህ ሁሉ ከሆነ በኋላ ምንም እንደማያውቅ ሰው እዚህ ፌስቡክ ላይ ህዝብን ማወናበድ ምንም አይሰራም፡፡ በአካል ያንን ሁሉ ካሉ በኋላ አቶ ተክሌም ሆኑ ሌሎች ደርሰው ለሀገር አሳቢ በመምሰል በአገርም በዘመድም የማይገናኝን ነገር በማገናኘት ኢህአፓና መኢሶን ቅብርጥሴ ማለት ትርፉ ትዝብት ነው፡፡

የዜጎችን ጥያቄ በግድያ ማስቆም አይቻልም (ሰማያዊ ፓርቲ)

May 7, 2014
ከሰማያዊ ፓርቲ የተሰጠ መግለጫ

የዜጎችን ጥያቄ በግድያ ማስቆም አይቻልም

በአሁኑ ወቅት ኢትዮጵያ ነጻ እንዲወጡ እገዛ ያደረገችላቸውን ጨምሮ አብዛኛዎቹ አገራት የህዝብን ጥያቄ በተገቢው የሚያዳምጡ፣ ችግሮች ሲኖሩ በጠረጴዛ ዙሪያና በሰከነ መልኩ መፍታት የሚችል መንግስት መመስረት ሲችሉ በተቃራኒው በአገራችን ስልጣን ላይ ያለው ህወሓት/ኢህአዴግ ግን ዜጎችን በኃይል እየገዛ ይገኛል፡፡ ለዚህም በቅርቡ በአገራችን የተለያዩ ክፍሎች የተፈጸሙትን ግድያዎችና ሌሎች ህገ ወጥ እርምጃዎች በምሳሌነት መጥቀስ ይቻላል፡፡Ethiopia's Semayawi (Blue) party logo
የአዲስ አበባና በዙሪያዋ የሚገኙት ከተሞች ‹‹የተቀናጀ መሪ ፕላን (ማስተር ፕላን)›› አስመልክቶ በስርዓቱ ላይ ጥርጣሬ የገባቸው የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ያነሱት ሰላማዊ ጥያቄ ተከትሎ በርካታ ተማሪዎችና ነዋሪዎች ህይወታቸውን አጥተዋል፡፡ ብዙዎቹ ቆስለዋል፡፡ በርካታ ተማሪዎች ለእስር ተዳርገዋል፡፡ በተያያዘ ከወራት በፊት በሀረር ከተማ የተከሰተውን ቃጠሎ ተከትሎም ዜጎች ላይ ተመሳሳይ እርምጃ ተወስዷል፡፡ በተመሳሳይ በባህር ዳርና ጎንደር ከተሞች ‹‹ህገ ወጥ ግንባታ ነው›› ተብለው ያለ ካሳ፣ ቅያሬና በቂ ጊዜ ቤታቸው የፈረሰባቸው ዜጎች ቤታቸው በዚህ ሁኔታ መፍረሱ አግባብ አለመሆኑን በመግለጻቸው በጥይት ተደብድበዋል፡፡ አብዛኛዎቹም ለከፋ ድብደባ ተዳርገዋል፡፡ ቀሪዎቹ በተለይም ጥያቄ ያነሳሉ ተብለው የተፈሩት አባወራዎች እስር ቤት ውስጥ ታጉረዋል፡፡
ዜጎች ጥያቄያችው ምንም ይሁን ምን ‹‹መንግስት ነኝ!›› ብሎ ስልጣን ላይ የተቀመጠ አካል ጥያቄያቸውን አዳምጦ በሰከነ መንገድ ምላሽ ወይንም መፍትሄ የመስጠት ግዴት የነበረበት ቢሆንም ዜጎችን ምንም አይነት ጥያቄ እንዲያነሱ የማይፈልገው ገዥው ፓርቲ ምላሹ ለሰላማዊ ዜጎች የማይገባ ጥይት ሆኗል፡፡ ገዥው ፓርቲ የዜጎችን ጥያቄ በኃይል ለማፈን የሚሞክረው ለዜጎች መሰረታዊ ጥያቄን አሟልቶ አገር የመምራት ብቃት የሌለው ከመሆኑ አንጻር ህዝብ ሌሎች በርካታ ጥያቄዎችን ያነሳብኛል ብሎ ስለሚሰጋ፣ የተነሱትንም ጥያቄዎች የመመለስ አቅም ስለሌለውና ምንም አይነት ችግር ቢኖርም ህዝብ እያስፈራራ ለመግዛት ካለው አባዜ ነው፡፡
ይህ ስርዓቱ የራሱን መሰረታዊ ጥያቄዎች በሰላማዊ መንገድ መመለስና መፍታት ሲያቅተው ህዝብን በኃይል አፍኖ የመግዛት የፖለቲካ ባህሉም አገራችን ከመቼውም ጊዜ በላይ ወደ በፖሊስ መንግስትነት (ፖሊስ ስቴት) ስር እንደወደቀች ዋነኛ ማሳያ ነው፡፡ በዚህ የስርዓቱ ባህሪ ምክንያት ኢትዮጵያ አገራችን ዜጎች ሰላማዊ ጥያቄያቸውን ለመንግስት የማያቀርቡባት፣ ጥያቄያቸውን ሲያቀርቡም ህይወታቸውን የሚያጡባት አገር እንደሆች የሰሞኑ አረመኔያዊ እርምጃን በምሳሌነት ማንሳት ይቻላል፡፡
ዜጎች የትኛውንም ጥያቄ በሰላማዊ መንገድ ማንሳት መብታቸው እንደሆነ የሚያምነውና ለዚህም የሚታገለው ሰማያዊ ፓርቲ ስርዓቱ በተለያዩ የአገራችን ክፍሎች እየፈጸማቸው የሚገናቸውን አረመኔያዊ እርምጃዎች ያወግዛል፡፡ እስካሁን ድረስ ገዥው ፓርቲ በኢትዮጵያውያን ላይ የወሰደውን እርምጃ ህጋዊ ለማስመሰል የባንክ ዘረፋንና ህገ ወጥ የቤት ግንባታን የመሳሰሉትን ምክንያቶች በመጥቀስ የተወሰደውን እርምጃ ህጋዊ ለማድረግ መሞከሩም ተጠያቂነት የጎደለውና ከምክንያት የራቀ በመሆኑ፤ እነዚህ ዜጎች ላይ የተወሰደውን እርምጃ ላይ ለህዝብ በቂ መረጃ እንዲሰጥና ተጠያቂነቱን እንዲወስድ እናሳስባለን፡፡
ህወሓት/ኢህአዴግ የአገራችንን ህዝብ ጥያቄ በኃይል ለመደፍጠጥ ቆርጦ የተነሳ በመሆኑ የትኛውንም ሰላማዊ ጥያቄ ያነሳ ኢትዮጵያዊ ላይ ተመሳሳይ እርምጃ እንደሚወስድ በተደጋጋሚ ታይቷል፡፡ በመሆኑም ኢትዮጵያውያን ገዥው ፓርቲ በፈጠረው የከፋፍለህ ግዛ ስርዓት ሳይወናበዱ በዜጎቻችን ላይ የሚደርሰውን ህገ ወጥ እርምጃ ላይ ድምጻቸውን እንዲያሰሙና ለስርዓቱ መሳሪያ ከመሆን እንዲቆጠቡ እንዲሁም አገር በቀልና ዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብት ተቋማት፣ የሚዲያ ተቋማት፣ የፖለቲካ ድርጅቶችና ሚዲያዎች ገዥው ፓርቲ በህዝብ ላይ እየወሰደው ያለውን የኃይል እርምጃ እንዲያጋልጡና እንዲቃወሙ፣ እያጋለጡና እየተቃወሙ ያሉትም አጠናክረው እንዲቀጥሉ ሰማያዊ ፓርቲ ያሳስባል።