June 3rd, 2014
ትዝ ይለኛል በ1997 ዓ.ም ይወጡ ከነበሩ ፕሬሶች ‹‹ነፃነት›› ጋዜጣ ትመስለኛለች በፊት ለፊት ገጽዋ ‹‹ንቢቱ መናደፍ ጀመረች!!›› የሚል ርዕስ ይዛ ነበር፡፡ የመለስን ‹‹እንከን የለሽ ምርጫ እናካሂዳለን›› የአደባባይ ቃል በጥይት ለመቀልበስ ሲሞከር የተሰጠ ርእስ ነበር፡፡
እነዚህ ሰዎች በርግጥም ዴሞክራሲን በወረቀት እንጂ በተግባር ለማረጋገጥ አልቻሉም፡፡ በአንድ እጃቸው ምዕራባዊያን እንዳይከፋቸው ዴሞክራሲን በሌላ እጃቸው ደግሞ የዴሞክራሲ መቀልበሻ ክላሽ ይዘው 23 ዓመታትን አስቆጥረዋል፡፡
አሁንም ዴሞክራሲንና ክላሽን አንግተው ሁለቱንም እንዳስፈላጊነቱ እየተጠቀሙ ይገኛሉ፡፡ ሁለቱ ግን ፈፅሞ የሚቀላቀሉ አይደሉም፡፡ ከሁለቱ አንዱን መምረጥ ያስፈልጋል፡፡ ኢህአዴግም አንዱን መምረጥ አለበት፡፡
አንደኛው ምርጫ ክላሹን ለድንበር መጠበቂያ ብቻ በማድረግ ዴሞክራሲያዊ ስርዓት ሳይሸራረፍ እንዲረጋገጥ ማድረግ ነው፡፡ አፈና፣ ዛቻ፣ ማስፈራሪያ፣ እስርና ግድያን በማቆም ስልጣን ከምርጫ ኮሮጆ ብቻ እንዲወጣ ማድረግ ነው፡፡
ይህንን ማድረግ ካልቻለ ሁለተኛ ምርጫም አለው፡፡ ደፈር ብሎ ‹‹ከዚህ በኋላ ምርጫ፣ መድብለ ፓርቲ፣ ነፃ ፕሬስ፣ በነፃ መደራጀት፣ መቃወም አይቻልም፡፡ መፃፍም አይቻልም፡፡ ያለውም አንድ ፓርቲ ብቻ ነው፡፡ አብዮታዊ ዴሞክራሲ ወይም ሞት…›› የሚል አዋጅ አውጆ ቢያርፈው፡፡ ሶቅራጥስ እንዳለው ዓለም በሁለት ተቃርኖዎች ውስጥ ናት፡፡ ኢህአዴግም ከሁለቱ ተቃርኖዎች (ዴሞክራሲና ጠመንጃ) አንዱን መምረጥ አለበት፡፡ እኛም ቁርጡን አውቀን እንቀመጥ ነበር፡፡
No comments:
Post a Comment